Monday, April 14, 2014

ወያኔ የትግራይን ሕዝብ ፈጠረ ወይስ የትግራይ ሕዝብ ወያኔን?

April 14/2014

(ሠዓሊ አምሳሉ ገብረኪዳን አርጋው)
TPLF-Logo


እንደሚታወቀው በሕወሓት የትጥቅ ትግል ዘመን የትግራይ ሕዝብ ከሞላ ጎደል ሊባል በሚችል ደረጃ ለሕወሓ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ያደርግ ነበር፡፡ ይሄንን ዓይነት ገደብ የለሽ ድጋፍ የትግራይ ሕዝብ ለሕወሓት እንዲሰጥ ያደረጉት ዋና ዋና ምክንያቶች ተብለው ሲጠቀሱ የምንሰማቸው፡-
  1. የሕወሓት ታጋዮች ልጆቹ የአብራኩ ክፋይ ስለሆኑ፡፡
  2. ወያኔ የትግራይ ሕዝብ ለደርግጥላቻ እንዲኖረውና ከጎኑ እንዲሰለፍ ለመድረግ ደርግ በሕዝቡ ላይ የፈጸመው አስመስሎ የፈጸማቸው የግፍ ሴራዎች ስለሰመሩለት
  3. ሕወሓት ለትግራይ ሕዝብ ‹‹ወደፊት እንዲህ እንዲህ አደርጋለሁ›› ብሎ ቃል በመግባቱና በሕዝቡም በመታመኑ፡፡
  4. እንደነሱ አገላለጽ “ኢትዮጵያ ውስጥ ለሺህዎች ዓመታት በነበረው አገዛዝ ተረግጠው፣ ተንቀው፣ በማንነታቸው እንዲያፍሩ፣ እንዲሸማቀቁ፣ የበታችነት ስሜት እንዲሰማቸው በመደረጉ እንደዜጋ ባለመታየታቸው መብታቸውን እኩልነታቸው ንለማረጋገጥ”
  5. አሁንም እንደእነሱ አገላለጽ በ3ኛ ደረጃ ያለውን ማሳካት ካልተቻለ የሕወሓት ስሙ እንደሚያመለክተው ትግራይን ነጻ አውጥቶ (ገንጥሎ) የትግራይን ሕዝብ ከጭቁን ብሔረሰብነት ነጻ ለመውጣት፣ …ወዘተ እያሉ ይዘረዝራሉ፡፡ እኔ ግን ለአሁኑ በ3ኛ ደረጃ ላይ የተጠቀሰችውን ጉዳይ ብቻ ላንሳ፡፡
በተለይ ሕወሓት ኢሕአዴግ ሥልጣን ከያዘ ወዲህ በትጥቅ ትግሉ ወቅት ከነበረውም ድጋፍ ይልቅ ሙሉ ለሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ ሕወሓት የትግራይን ሕዝብ ድጋፍ ለማግኘት ችሏል፡፡ ሕወሓት ይሄንን ውለታውን ለመመለስና አስቀድሞ የገባውንም ቃል ለመፈጸም ሲል “ቅድሚያ በጦርነት ለተጎዳ ክልል” በሚል መርሕ በመጀመሪያዎቹ የሥልጣን ዘመናቱ ሁሉም ነገር ወደ ትግራይ ይጋዝ ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ መንግሥት ጭራሽም በኦፊሴል(በይፋ) እንዲህ ዓይነት መርሕ አውጥቶ ልዩ ትኩረትና ድጋፍ ለአንድ ክልል ብቻ ለማድረግ ለመጥቀም የመሞከሩ ኢፍትሐዊነት፣ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ከመላ ሀገሪቱ በዚህ የተራዘመ ጦርነት ያልተጎዳ የሀገሪቱ አካባቢ ባለመኖሩ፣ ይልቁንም በተለያየ መልኩ ሲታይ ያ አካባቢ በዚያ ወቅት ከሌሎቹ የሀገሪቱ አካባቢዎች ተለይቶ ተጠቃሚ የነበረባቸውም ሁኔታዎች እንደነበረ ሲገለጥ እንዲህ እንዲህ ዓይነቱ ሙግት ከውጭም ከውስጥም ሲገጥመው ለይስሙላ ያህል ይህ መመሪያ እንደታጠፈ በመግለጽ ከዚያ በኋላም በስውርና በግልጽም እንደ ኤፈርት ያሉ በሀገሪቱ የኢንቨስትመንት (የመዋዕለ ንዋይ ፍሰት) ታሪክ ከፍተኛና ተወዳዳሪ የሌለው የንግድ ተቋማትን በማደራጀት ትግራይን ከሌሎቹ የሀገሪቱ አካባቢዎች በተለየ መልኩ በልዩ ትኩረት የማልማት ከፍተኛ እንቅስሳሴ ሲያደርግ ቆይቷል እያደረገም ይገኛል፡፡
በዚሁ አንጻር በተለያዩ ጉዳዮች ሁሉ የትግራይ ሕዝብ ልዩ ትኩረትና ቅድሚያ እየተሰጠው ተጠቃሚ ሲሆን ቆይቷል እየተጠቀመም ይገኛል፡፡ ይሁንና ወያኔ የተቻለውን ያህል ከዚያም በላይ ርብርብና የሀብት ፍሰት በትግራይ ላይ ቢያደርግም የሕዝቡን ወይም የትግራይን ፍላጎት ሊሟላ እንዳልቻለ ከሕዝቡ የሚቀርብ ቅሬታ ያመለክታል፡፡ ይለዋል ይለዋል ያፈሰዋል ያፈሰዋል እንደ ቀዳዳ ከረጢት ትግራይ ግን አየሁኝ አትልም ሕዝቡም ቅም አላለው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በተቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህ ቅጥና ልክ ያጣ ዐይን ያወጣ ኢፍትሐዊ አድልኦ ቅሬታ ከማስከተል አልፎ በተለያዩ መንገዶች የሚገለጹ ተቋውሞዎችን አስከተለ፡፡ በዚህ መሀል ሕወሓት ለሁለት ተሰነጠቀና የትግራይ ሕዝብ ከሕወሓት ሌላ አማራጭ የማግኘት ዕድል አጋጠመው ለዚህ አዲስ ለተፈጠረ አካልም የትግራይ ሕዝብ ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ እያደገ የሚሄድ ድጋፍ መስጠቱን ቀጠለበት፡፡ ሕዝቡ ለአዲሱ አማራጭ ድጋፍ የሚሰጥበት ሕወሓትን ደግሞ ያኮረፈበት የከዳበት ምክንያቶች ምን እንደሆነ ሲገልጽ ሁሉም በአንድ ድምፅ የሚገልጸው ጉዳይ ሕወሓት በትጥቅ ትግሉ ወቅት ቃል የገባልንን ጉዳይ እስከዛሬም ድረስ ቢሆን አላሟላልንም የሚል እንደሆነ ይገለጻል፡፡ ይታያቹህ ሕወሓት ኢሕአዴግ የተቀረው የሀገሪቱ ክፍል እየደማ ሕዝብ እያለቀሰ ትግራይን እያለማ የተቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ ምን ይጎዳል ሳይል ሲኳትንላቸው ኖሮም የገባውን ቃል አላሟላልንም ለመባል በቃና አረፈው፡፡
arena-tigray-logoእኔ በግሌ ሕወሓት ለሁለት ተሰንጥቆ አረና ትግራይ የሚባል ፓርቲ ሲፈጠር ኢትዮጵያዊነት የሚሰማው ፓርቲ ከትግራይ አገኘን የሚል እምነት ነበር ያደረብኝ፡፡ ከፓርቲው ዓላማና ግብ መረዳት የምንችለውም ይሄንኑ ነበር፡፡ ነገር ግን በተለያዩ አጋጣሚዎች ሁሉም ባይሆኑም የአረና ፓርቲ አመራሮች ሕዝቡ በወያኔ ላይ ያነሣውን ቅሬታ እነሱም ተጋርተው ደግመው ሲያነሡት ስሰማ፤ አሃ ከመጋረጃ ጀርባ ያለው ጨዋታ ሌላ ነው ማለት ነው? እንድል አደረገኝ፡፡ ለምሳሌ አቶ ዐሥራት አብርሃ ከኢሳት ሬዲዮና ቴሌቪዥን (ነጋሪተ ወግና ምርዓዬ ኩነት) ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፣ አቶ ገብሩም እንደዚሁ ለቪኦኤ በሰጡት ቃለ መጠይቅ ሌሎችም በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲያነሡት እንደሰማነው የትግራይ ሕዝብ በወያኔ እንደተከዳ ይናገራሉ፡፡ አቶ ዐሥራት ካሉት ብጠቅስ፡- “የትግራይ ሕዝብ አሉ አቶ ዐሥራት የትግራይ ሕዝብ ወያኔ ከገባልን ቃል አልፈጸመልንም ከሚለው ለምሳሌ አንዱ በወሎ በኩል የትግራይ ድንበር “አለ ውኃ”  ምላሽ ነው ብሎ ያምናል ሕዝቡ ይሉና አቶ ዐሥራት ወያኔ ግን እስከዛሬ ድረስ ይሄንን ድንበር አላስመለሰም” በማለት በቁጭትና በብስጪት ያነሣሉ፡፡
የአረና ፓርቲ ይሄን ጉዳይ በተመለከተ እንደፓርቲ በተለያየ ጊዜ በአመራሮቹ ከተገለጸው የተለየ ከሆነ አቋሙን በመግለጽ የተፈጠረውን ብዥታ እንዲያጠራ በዚህ አጋጣሚ ማስገንዘብ እወዳለሁ፡፡ (ይህ ወሰን ተካለለ የሚባለው በ1801ዓ.ም. አካባቢ በስግብግብነታቸው በሚታወቁት በትግሬው መስፍን ራስ ወልደ ሥላሴ ከወረሴኸች መሳፍንት ጋር በመስማማት እንደሆነ የትግራይ ሽማግሎች ይናገራሉ) ቀጠል አድርገውም አቶ ዐሥራት በአፋርም በኩል እንዲሁ የትግራይ መሬት አልተመለሰም ይላሉ፡፡ ይህ የትግራይ ሕዝብ ቅሬታ በአረና ትግራይ የፓርቲው አመራሮችም መነሣቱ ምን ማለት እንደሆነ የገባው ሕወሓት ይሄንን ቅሬታ ለመፍታት እነደገና ከ23 ዓመታት በኋላ ጥድፊያ ውስጥ በመግባት ከአፋር ከነባ ወረዳን ቆርሶ ወደ ትግራይ መከለሉን እዚያው ላሉ የአፋር ነዋሪዎች ሲያስታውቅ ቀድሞ ከተከለለው በተጨማሪም አዳዲስ መሬቶችን ከጎንደርና ከወሎም ወደ ትግራይ እንዲሁ መከለሉን ለማወጅ ዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡ ከጎንደር የተወሰደው መሬት ታች ድረስ ወርደው ራስ ዳሸንንና አካባቢውን እንደሆነ የአካባቢውን ሕዝብ ለማግባባት ከተደረገው ሙከራ መረዳት ተችሏል፡፡ አፋሮቹ ክለላውን ወይም የመሬት ነጠቃውን በጸጋ ሳይቀበሉት ቀርተው ሰሞኑን ከፍተኛ ግጭት መነሣቱ ይታወቃል፡፡ በጎንደርና በወሎም በኩል የሚያጋጥመው ከዚህ የተለየ አይሆንም፡፡ አቤት አቤት ተነሥቶ የማይወሰድ ነገር መሆኑ ምንኛ በጀን ጃል? ምን ይተውልን ነበር? ዐይን ያወጣ ዘረፋ!
እንደሚታወሰው ሁሉ ወያኔ ሥልጣን ከመያዙ ከጎንደር ቆርሶ ወደ ትግራይ በከለለው መሬት ከገዛ ታጋዮቹም ጭምር ምን ያህል ተቋውሞ እንዳሥነሣ የሚታወቅ ጉዳይ ነው፡፡ ለምሳሌም በሰሜን አሜሪካ የሚኖሩ የወልቃይት ተወላጆች በ“መንግሥት” ሥራ በአሜሪካን ሀገር የሚኖሩ የወያኔ ታጋዮች ባስተባበሩት ሰላማዊ የተቋውሞ ሰልፍ ላይ እኛ የወልቃይት ተወላጆች የጎንደር አማሮች እንጂ ትግሬ አይደለንም፣ ማንነታችን ይጠና፣ ቋንቋ ስለተናገርን ብቻ ትግሮች ተደርገን መቆጠር የለብንም፣ እሱ ራሱን የቻለ ሌላ ምክንያትና ታሪካዊ ገጠመኝ አለው፡፡ በማለት በተቋውሞ ሰላማዊ ሰልፋቸው ላይ ማሰማታቸው ይታወሳል፡፡
እዚህም በሀገር ውስጥ ወልቃይቶች ጎንደር ከተማና ባሕር ጋር ድረስ በመምጣት በኃይለኛ ቅጣት እንዲያቆሙ እስከተደረጉበት ጊዜ ድረስ ተቋውሞዋቸውን በተደጋጋሚ ሲያሰሙ ቆይተዋል፡፡ በወሎም በኩል ተቆርሶ በተከለለው መሬት ሳቢያ ብዙ ተቋውሞ ደርሶ እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ይህ ጉዳይ ጊዜ እየጠበቀ እንጂ የመጨረሻ እልባት አግኝቶ አይደለም፡፡ እንግዲህ ያ ሁሉ ቀውስና ተቋውሞ በነበረበት ሁኔታ ነው የትግራይ ሕዝብ አልበቃኝም ገና ምኑ ተያዘና በገንዘብም በንብረትም በመሬትም በኩል ገና ብዙ ይቀራል እያለ ሕወሐትን የገባሀውን ቃል ገና አላስገባህም በማለት በወያኔ ላይ ተቋውሞ እያሰማና ጫና እያሳደረ የሚገኘው፡፡ እናንተዬ የትግራይ ሕዝብ ይህ አለ የሚባለው ነገር እውነት ከሆነ ከዚህ እሬት እሬት ካለን ወያኔ በላይ ሌላ የከፋ ወያኔ ነው ማለት ነው የሚፈልገውና የሚመኝልን? እግዚኦ በሉ ወገኖቸ፡፡ ይሄ ጤነኝነት ነው ትላላቹህ ? እኛ ትክሻችን ሳስቶ የወያኔን ቀንበር መሸከም አቅቶን ጎብጠን ባፍ ጢማችን ልንደፋ ሰኞ ሰኞ እያልን የትግራይ ሕዝብ ገና ምኑ ተያዘና ቃልህን አላከበርክም አምጣ አምጣ እያለ ቀንበር ያጸናብናል? ምን ነው እንተሳሰብ እንጂ? እንደ ሀገርና ሕዝብ አስቡ እንጂ? ስለዚህ ወያኔን የትግራይ ሕዝብ ፈጠረ እንጂ ወያኔ የትግራይን ሕዝብ አልፈጠረማ? ይሄኔ ነው መንቃት አለያገሬ ሰው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ ሕዝብና የፖለቲካ ፓርቲዎች ከወያኔ ጋር ስላሉብን ችግሮች መደራደር ካለብን መደራደር ያለብን ከትግራይ ሕዝብ ጋራ ነው ማለት ነዋ? ወያኔ የፈጠረብን ችግሮች ሁሉ በወያኔ መወገድ አብረው የሚወገዱና የሚፈቱ አይደሉም ማለት ነዋ? ገና ወያኔ ከዚህም የከፋ እንዲሆን ወይም ከወያኔም የከፋ ሌላ ወያኔ ይጠብቀናል ማለት ነዋ? ለኢትዮጵያ ሕዝብ ከዚህ የከበደ መርዶ ይኖራል ብየ አላስብም፡፡ ለእንደዚህ ዓይነት የእሳት ላይ ጨዋታም ዝግጁ ይሆናል ብየ አልጠብቅም፡፡
ሲጀምር እኔ ግራ የሚገባኝ ነገር ወያኔ ከየት አምጥቶ ሊሰጥ ቃል እንደገባ፣ የትግራይ ሕዝብም ወያኔን ከየት አምጥቶ ይሰጠናል ብሎ እንደሚጠብቅ ነው፡፡ በእርግጥ ወያኔ የመንግሥትን ሥልጣን እንደመያዙ ሲያደርገው እንደቆየው ሁሉ የሀገሪቱን ሀብት እየዘረፈ ሊያፈስላቸው ይችላል ነገር ግን እንደ የኢትዮጵያ ሕዝብ አካልነቱ የትግራይ ሕዝብ እንዴት እንደዚህ ያስባል? እንዴት በእንደዚህ ዓይነቱ ሕገ ወጥ ኢፍትሐዊና አስነዋሪ በሆነ መንገድ በዝርፊያ የመጠቀም የመበልጸግ ፍላጎት ሊያድርበት ቻለ? ይሄ እኮ የወረደና የወደቀ የሞራል (የግብረ ገብ) እና የሥነ ምግባር ደረጃ ነው፡፡
በዚሁ አጋጣሚ የትግራይን ሕዝብ በተመለከተ ያለኝን ቅሬታና ሥጋት እንድገልጽ ከተፈቀደልኝ ወገን ሆይ! ስሜትህ ፍላጎትህ ምኞትህ ኢትዮጵያዊ አይደለም ወይ? ኢትዮጵያዊ የሆነ ፍላጎት ምኞትና አስተሳሰብ ያለው ወገን ከሌሎቹ የሀገሪቱ ክፍሎች ከወንድሞቹ እየተዘረፈ በሚመጣ ሀበትና ንብረት ልገንባ ልበልጽግ ብቻየን አላግባብ ልጠቀም ይላል ወይ ? በየትኛውም የሀገሪቱ አካባቢ ያለው የሀገሪቱ መሬት የሱም መሆኑን እረስቶ በግራ ቀኙ ለትውልድ ደም መፋሰስን ሊያስከትል በሚችል ድፍረት ጊዜ ሰጠኝ ብሎ ያለ ድርሻው ያለ ርሥቱ በግራና በቀኝ በታችና በላይ እየተንገበገበ ልስፋ ልስፋ ይላል ወይ? እኔ እንደሚገባኝ ኢትዮጵያዊ አስተሳሰብ ማለት ልክ እንደ አንድ ሀገር ሕዝብ ሁሉ ሁላችንም በፍትሐዊነት በእኩልነት አብረን እንልማ እንበልጽግ የጋራ ሀገራችንን እናሳድግ ማለት እንጂ ዘርፎ ወደ አንዱ እንደሚሄድ የሽፍታ መንጋ መስበድበዱ አይደለም፡፡ ለዚህ ኖሯል እንዴ ትግሉ? እኛ እኮ ለፍትሕ ለእኩልነት መስሎን ነበር እንጂ መች ለዚህ መሰለን፡፡ ይሄማ ከሆነ በዚህ የተማረረ ሌላው ሕዝብ ደግሞ እንደገና ሲሸፍት የተረፈብኝን ላስመልስ ሲል የዝርፊያ አዙሪት ውስጥ ገባን ማለት አይደለም እንዴ? ሰላም የሚባል ነገር ከዚህች ሀገር እንደራቀን መቅረቱ አይደለም ወይ?
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!
ዕንቁ መትሔት ቁጥር 115 ሚያዝያ 2006.ም.

No comments:

Post a Comment